ዜና
በመዲናዋ ለ5 ቀናት ሲካሄድ የቆየው የልማት ስራዎች የፎቶ አውደ-ርዕይ በዛሬው ዕለት በድምቀት ተጠናቋል።
28 ሚያዝያ 2018
በአዲስ አበባ ከተማ አሰተዳደር ኮሙኒኬሽን ቢሮ አዘጋጅነት "የእርጅና ገፅታን የገፈፈ ፤የውበት ፀዳል ያላበሰ" በሚል መሪ ቃል ባለፉት አምስት አመታት በአዲስ አበባ ከተማ የተከናወኑ የልማት ስራዎችን ለህዝብ ሲያስተዋውቅ የቆየው የፎቶ አውደ-ርዕይ በዛሬው ዕለት ተጠናቋል።
ከመጋቢት 23 ቀን ጀምሮ ለተከታታይ አምስት ቀናት ክፍት ሆኖ የቆየው ይህ አውደ-ርዕይ የከተማዋን ሁለገብ ለውጥ የሚያሳዩ በርካታ ምስሎች ለአንባቢያንና ለተመልካች እንዲቀርቡ የተደረገበት ነው።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ሃፍታይ ገብረእግዚአብሔር እንደገለፁት አውደ ርዕዬ ከለውጡ ወዲህ ባሉት አምስት ዓመታት መንግስት ለህዝብ የገባውን ቃል በተግባር መፈጸሙን፣የተመዘገቡ የልማት ውጤቶችንና የከተማዋን ጉዞ በተጨባጭ ለማሳየት ያለመ እንደነበር ተናግረዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ ኮሙኒኬሽን ቢሮ በመንግስትና በህዝብ መካከል ጠንካራ የኮሙኒኬሽን ሥርዓት በመዘርጋት በቂ መረጃ ያለውና በልማት ስራዎች ላይ ንቁ ተሳትፎ የሚያደርግ ማህበረሰብ ለመፍጠር እየሰራ እንደሚገኝም አቶ ሃፍታይ ገብረእግዚአብሔር አክለዉ ገልፀዋል።
አውደ ርዕዩ በመዲናዋ የሚኖሩ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ያሳተፈ ሲሆን ጎብኚዎች በመዲናዋ የታዩትን የመሠረተ ልማት ግንባታዎች ፣ የሰው ተኮር ስራዎችንና የከተማ ውበት ስራዎችን በፎቶ አውደ-ርዕይ ሲመለከቱ መሰንበታቸው ተገልፃል።
በማጠቃለያ መርሃ ግብር ላይ አስተያየታቸውን የሰጡት የጉብኝቱ ተሳታፊዎች በበኩላቸዉ አዲስ አበባ እውነትም በየጊዜው አዲስ ለውጥ እና ፈጣን እድገት የሚታይባት ከተማ እየሆነች መምጣቷን ተናግረዋል።
በተለይም ልማቱ የከተማዋን ገፅታ ከማሳመር ባለፈ ነዋሪውን ማዕከል ያደረገ ፍትሐዊ ተጠቃሚነት ያረጋገጠ መሆኑን የፎቶ አውደ-ርዕዬ ተሳታፊዎች ጠቁመዋል።